እስላማዊ መንግሥት በኢራቅ እና ሶሪያ (አይሲስ) የተመሠረተው ከአል-ቃዒዳ በኢራቅ (ኤኪውአይ) ፍርስራሽ ነበር፡፡ ይህ ቡድን የሶሪያን ግጭት ለማካተት እንቅስቃሴዎቹን ሲያሰፋ አይሲስን ተጠቅሟል፡፡ አይሲስ ደግሞ ይመራ የነበረው በአቡ በከር አል-ባግዳዲ ሲሆን፤ እርሱም በሰኔ 2006 ዓ.ም. እስላማዊ መንግሥት መቋቋሙን አወጀ፡፡ አል-ባግዳዲ በጥቅምት 16 ቀን 2012 ዓ.ም. እርሱን ለመያዝ በዩናይትድ ስቴትስ በተፈተጸመ ኦፕሬሽን ተገድሏል፡፡ አይሲስም በሶሪያ የነበረውን ግጭት እና በኢራቅ በጎሳዎች መካከል የነበረውን ውጥረት ተጠቅሞበታል፤ ይህም ደግሞ በሁለቱም አገራት ግዛቶችን ለመቆጣጠር አስችሎታል፡፡ በ2011 ዓ.ም. በርካታ አጋር አገራትን እና ዓለም ዓቀፍ ተቋማትን ያካተተው ጥምረት አይሲስ በሶሪያ እና ኢራቅ የተቆጣጠራቸውን ግዛቶች እንዲለቅ አድርገውታል፡፡ በኢራቅ፣ ሶሪያ እና በሌሎች አገራት በዚህ ቡድን ላይ የሚካሄዱ ጥረቶች ቀጥለዋል፡፡
በኅዳር 2007 ዓ.ም. አይሲስ በፓሪስ የተቀናጁ ጥቃቶች ፈጽሞ ከሞላ ጎደል 130 ሰዎች ተገድለዋል፤ ከእነርሱም መካከል አንድ አሜሪካዊ ይገኝበታል፤ ሌሎች ከ350 በላይ የሚሆኑ ደግሞ ቆስለዋል፡፡ በመጋቢት 2008 ዓ.ም. አይሲስ በብራስልስ በተመሳሳይ ሰዓት ሁለት ጥቃቶች ፈጽሞ የአሜሪካ ዜጎችን ጨምሮ 32 ሰዎች ሞተዋል፤ ከ250 በላይ ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል፡፡ በሰኔ 2008 ዓ.ም. ለአይሲስ ታማኝ መሆኑን የገለጸ አንድ ታጣቂ በኦርላንዶ በሚገኝ ፐልስ በተባለ ጭፈራ ቤት 49 ሰዎችን ገድሎ ሌሎች 53 የሚሆኑትን ደግሞ አቁስሏል፡፡ በ2011 ዓ.ም. የፋሲካ ወቅት በሲሪ ላንካ አምስት የአሜሪካ ዜጎችን ጨምሮ ከ250 በላይ ሰዎች ተገድለዋል፤ ይህም የሆነው በአይሲስ የተበረታቱ ሰዎች በበርካታ አብያተ ክርስቲያናት እና ሆቴሎች ላይ ጥቃት በፈጸመበት ወቅት ነበር፡፡
በታኅሳስ 08 ቀን 1997 ዓ.ም. የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አል-ቃዒዳ በኢራቅ (አሁን አይሲስ በመባል የሚታወቅ) በተሻሻለው የኢምግሬሽን እና ዜግነት ሕግ፣ በክፍል 219 መሠረት በውጭ አገር የሚገኝ ሽብርተኛ ድርጅት ብሎ ሰይሞታል፡፡ ቀደም ሲል በጥቅምት 05 ቀን 1997 ዓ.ም. የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አል-ቃዒዳ በኢራቅ ልዩ አለም አቀፍ ሽብርተኛ በማለት በስራ አስፈፃሚ ትእዛዝ (ኤክዘኪውቲቭ ኦርደር) 13224 እንደተሻሻለው መዝግቦታል፡፡ በዚህም መሰረት በዩናይትድ ስቴትስ አስተዳደር ወሰን ውስጥ የሚገኙ የአል-ቃዒዳ በኢራቅ ንብረቶች እና ጥቅሞች ሁሉ ታግደዋል፣ ማናቸውም የዩናይትድ ስቴትስ ሰዎች ከአል-ቃዒዳ በኢራቅ ጋር በምንም አይነት ልውውጥ ላይ መሳተፍ አይፈቀድላቸውም፡፡ በተጨማሪም በዩናይትድ ስቴትስ በውጭ አገር የሚገኝ ሽብርተኛ ድርጅት በሚል ለተመዘገበው አይሲስ ሆን ብሎ የማቴሪያል ወይም የሀብቶች አቅርቦት ማድረግ፣ ወይም ለማቅረብ መመሳጠር የተከለከለ ወንጀል ነው፡፡