ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን (ቲቲፒ) በ1999 ዓ.ም. የተመሠረተ የፓኪስታን እና አፍጋኒስታን ሽብርተኛ ድርጀት ነው፡፡ ዓላማውም በሽብር ድርጊቶች የፓኪስታንን መንግሥት ከኻይበር ፓኽቱንከዋ ክፍለ አገር (በይፋ በፌደራል መንግሥት የሚተዳደሩ የጎሳ አካባቢዎች ተብሎ የሚጠራ) ማስወጣት እና የሸሪዓ ሕግ አስተዳደርን መመሥረት ነው፡፡ ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን ርዕዮተ ዓለማዊ ምሪት የሚያገኘው ከአል-ቃዒዳ ሲሆን፣ የአል-ቃዒዳ አካላት ደግሞ በአፍጋኒስታን እና ፓኪስታን ድንብር በተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን ጥበቃ ይደረግላቸዋል፡፡ ይህ ሁኔታም ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን የአል-ቃዒዳ የሽብር ኔትወርክ ተደራሽ እንዲሆንለት እና የአባላቱ የእንቅስቃሴ ሙያን እንዲቀስም አስችሎታል፡፡
ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን (ቲቲፒ) ለበርካታ በፓኪስታን እና በዩናይትድ ስቴትስ ጥቅሞች ላይ ለተፈጸሙ የሽብር ድርጊቶች ኃላፊነት ወስዷል፤ ከእነዚህም መካከል በታኅሳስ 2001 ዓ.ም. በኾስት፣ አፍጋኒስታን የአሜሪካ የጦር ሰፈር ላይ የተፈጸመው የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት እንዲሁም በሚያዝያ 2002 ዓ.ም. በፔሻዋር፣ ፓኪስታን የተፈጸመው እና ስድስት የፓኪስታን ዜጎችን የገደለው በዩናይትድ ስቴትስ ቆንስላ ላይ የተፈጸመ የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት ይካተታሉ፡፡ ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን በቀድሞ የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስቴር ቤናዚር ቡቶ ላይ በ1999 ዓ.ም. የተፈጸመው ግድያ ላይ ሳይሳተፍ አይቀርም ተብሎ ይጠረጠራል፡፡ ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን በሚያዝያ 23 ቀን 2002 ዓ.ም. በኒው ዮርክ ከተማ ታይምስ አደባባይ በፈይሰል ሻሃዛድ የተሞከረው እና ያልተሳካው ፈንጂ የማፈንዳት ሙከራ መርቷል፣ አመቻችቷል፡፡
በነሐሴ 26 ቀን 2002 ዓ.ም. የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን (ቲቲፒ)ን በተሻሻለው የኢምግሬሽን እና ዜግነት ሕግ፣ በክፍል 219 መሠረት በውጭ አገር የሚገኝ ሽብርተኛ ድርጅት እንዲሁም ልዩ አለም አቀፍ ሽብርተኛ በማለት በስራ አስፈፃሚ ትእዛዝ (ኤክዘኪውቲቭ ኦርደር) 13224 እንደተሻሻለው መዝግቦታል፡፡ በዚህም መሰረት በዩናይትድ ስቴትስ አስተዳደር ወሰን ውስጥ የሚገኙ የተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን (ቲቲፒ) ንብረቶች እና ጥቅሞች ሁሉ ታግደዋል፣ ማናቸውም የዩናይትድ ስቴትስ ሰዎች ከተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን (ቲቲፒ) ጋር በምንም አይነት ልውውጥ ላይ መሳተፍ አይፈቀድላቸውም፡፡ በተጨማሪም በዩናይትድ ስቴትስ በውጭ አገር የሚገኝ ሽብርተኛ ድርጅት በሚል ለተመዘገበው ተህሪክ-ኢ ታሊባን ፓኪስታን (ቲቲፒ) ሆን ብሎ የማቴሪያል ወይም የሀብቶች አቅርቦት ማድረግ፣ ወይም ለማቅረብ መመሳጠር የተከለከለ ወንጀል ነው፡፡